የተስማሚነት ምዘና በንግድ መድረክ
አዳዲስ ገበያዎችን ዘልቆ ለመግባት ደረጃዎችን መሰረት ያደገረ የተስማሚነት ምዘና አገልግሎት ወሳኝ ነው። ይህም ምርቶችና አገልግሎቶች ከሀገር ውስጥ ገበያ ባሻገር በዓለም ዓቀፍ ገበያ ተፈላጊነታቸውን እንዲጨምር የማይተካ ሚና ይጫወታል። የፍተሻ ላብራቶር፣ የኢንስፔክሽንና የሰርቲፊኬሽን አገልግሎቶች በጥቅሉ የተስማሚነት ምዘና አገልግሎት የሚባሉ ሲሆን ዓላማውም በገዥና ሻጭ መካከል ለሚፈጠር የንግድ ሂደት ነጻና ገለልተኛ የሦስተኛ ወገን መተማመኛ ሰነድ ሆኖ ያገለግላል። ይህም የመተማመኛ ሰነድ ምርቱ ወይም አገልግሎቱ በተቀመጠው የጥራት መስፈርት መሰረት ተፈትሾና ተረጋግጦ ስለሚሰጥና በዓለም አቀፍ ገበያ እንደመግባቢያ ስለሚያገለግል በሁሉም ቦታና ሀገራት ተቀባይነት እንዲኖረው ያደርጋል። ለምሳሌ፤ ቬትናምን ብንመለከት ምርቶቿ ከራሷ አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት እንዲኖራቸው አምራች ድርጅቶቿ በተስማሚነት ምዘና አገልግሎት የአሰራር ስርዓት እንዲያልፉ በማድረጓ ኢኮኖሚያዊ አቅሟን ማጠናከርና በንግዱ መድረክም ተወዳድራ እንድታሸንፍ ምክንያት ሆኗታል። በዚህ የአሰራር ሥርዓት ሀገሪቱም ከዚህ የሚከተሉትን ቁልፍ ጥቅሞች አግኝታለች።
የንግድ ተግዳሮቶቿ ተወግዶላታል
ባለንበት የሰለጠነ ዘመን ሀገራት የዜጎቻቸውን ጤንነት ለመጠበቅ የህግ ማዕቀፍ ማውጣት አስፈልጓቸዋል። ሆኖም የሕግ ማዕቀፉ ለዓለም አቀፍ ንግድ መሰናክል ሊሆን አይገባም። በዚህ ምክንያት ሀገራት የሚያዘጋጁት ቴክኒካል ሪጉሌሽን የዓለም አቀፍ ደረጃዎች ድርጅት (ISO) የሚያወጣቸውን ደረጃዎች መሰረት ያደረገ ሊሆን ይገባል። ይህም በውጤቱ ሀገራት ወደ ውጭ የሚልኳቸው ምርቶች በተመሳሳይ መስፈርት እንዲመዘኑና ተቀባይነት እንዲኖራቸው ያስችላል።
የፍተሻ ውጤቶቿ አመኔታን አግኝቶላታል
የተስማሚነት ምዘና አገልግሎት የምርት፣ የአገልግሎትና የአሰራር ሥርዓት የተቀመጠላቸውን የጥራት መስፈርት ማሟላታቸውን የሚረጋገጥበት ሂደት ሲሆን ይህም ተግባር በኦዲተሮች፣ በላቦራቶሮች፣ በኢንስፔክሽንና በሰርቲፊኬሽን ባለሙያዎች የሚከናወን በመሆኑ አሰራሩን ተዓማኒ ያደርገዋል። በዓለም አቀፍ የንግድ መድረክ እያንዳንዱ የፍተሻ ላቦራቶር ውጤት ከሌላው ሀገር ላቦራቶር ውጤት ጋር በንፅፅር በትክክልና በተመሳሳይ መንገድ መከናወናቸውን ማረጋገጥ ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ ዋነኛው መሳርያ በቀዳሚነት በዓለም አቀፍ ደረጃዎች ድርጅት (ISO) የተዘጋጀውን የላብራቶር የሥራ አመራር የአሰራር ሥርዓትን (ISO/IEC 17025 laboratory management system) በመተግበር ሀገራት ተመሳሳይ የፍተሻና የልኬት ሥርዓት እንዲኖራቸው አስችሏል።
ይህ የአሰራር ሥርዓት በተስማሚነት ምዘና አገልግሎት የሚሰጡ የፍተሻ ላቦራቶር ውጤቶች ተዓማኒና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እንዲሁም በወጪና ገቢ ንግድ ወቅት ሊኖር የሚችለውን የዳግም ፍተሻ ያስቀራል። በተጨማሪም ይህንን የአሠራር ሥርዓት ሀገሮች ከተለያዩ ሀገራዊ ፖሊሲዎቻቸው ጋር በማገናኘታቸው ተቆጣጣሪ አካላት በዚህ ደረጃ ዓለም አቀፍ እውቅና ማግኘትን እንደ ቀዳሚ መስፈርት አድርገውታል። ቬትናምም ይህንኑ ማድረግ በመቻሏ እና አምራች ድርጅቶቿም በዚሁ የአሰራር ስርዓት በማለፋቸው የተስማሚነት ምዘና ተቋሞቿ የሚያወጡት የፍተሻ ውጤት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት እንዲኖራቸው ከማስቻሉም ባሻገር ተቆጣጣሪ አካላት የተስማሚነት ምዘና ተቋሞቿ ከዓለም አቀፍ ሕግጋት ጋር መናበባቸውን እንዲያረጋግጡ ረድቷታል።
(ምንጭ ISO focus July-Aug 2016 edition page 30)
የስራ አካባቢ ደህንነት የሥራ አመራር ሥርዓት (ISO 45001 work place safety management system) ለምን ያስፈልጋል?
በዓለማችን ማንኛውም ሠራተኛ፣የስራ መሪም ሆነ ባለሀብት እንዲፈጠር የሚፈልጉት የጋራ ጉዳይ ቢኖር በስራ አካባቢ የሚከሰት አደጋ እንዲቀነስና የተሻለ የሥራ ቦታን እንዲፈጠር ነው።በመሆኑም ይህንን የጋራ ጉዳይ ለማሳካት ታቅዶ የተዘጋጀውን የስራ አካባቢ ደህንነት የስራ አመራር ስርዓት (ISO 45001 work place safety management system) በመተግበር እንዴት የሥራ ላይ አደጋን መቀነስና የተሻለ የሥራ አካባቢ መፍጠር እንደሚቻል መመልከቱ ተገቢ ነው።
ጥናቶች እንደሚጠቁሙት በቀን ውስጥ በየ15 ደቂቃው ቢያንስ አንድ ሠራተኛ ከስራ ጋር በተያያዘ በሚፈጠር አደጋ ወይም በሽታ የሚሞት ሲሆን 153 ሠራተኞች ደግሞ ከስራ ጋር በተያያዘ በሚፈጠር አደጋ አካል ጉዳተኛ ይሆናሉ። በዓለም አቀፍ ደረጃም ከሥራ ደህንነት ጋር በተያያዘ በሚፈጠሩ አደጋዎች በዓመት 2.8 ትሪሊየን ዶላር ኪሳራ ይመዘገባል። ይህ ደግሞ በተቋምና በሕብረተሰቡ ላይ ከፍተኛ ጫና ያሳድራል።
ሆኖም ግን ይህን ችግር ሊፈታ የሚችል የአመራር ስርዓት መዘርጋት የሚፈጠረውን አደጋ ለመቆጣጠር አይነተኛ መፍትሔ በመሆኑ የሥራ አካባቢ ደህንነት ሥራ አመራር ስርዓት (ISO 45001 Work Place Safty Management System) መገንባት አስፈላጊ ይሆናል። በመሆኑም ለሁሉም ተቋማትና ኢንዱስትሪዎች የአሰራር ስርዓቱን መተግበር ለሠራተኞች ለሥራ ምቹ የሆነ አካባቢ ከመፍጠሩም ባሻገር በሥራ ቦታ የሚፈጠሩ አደጋዎችን ለመከላከል ያስችላል።
በተጨማሪም በአምራች ወይም በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ስርዓቱ ከተዘረጋ ለሠራተኞች መልካም የስራ አካባቢ እንዲፈጠር መሰረት የሚጥል ሲሆን ለባለሀብቱ ደግሞ በስራ ላይ ለሚፈጠሩ አደጋዎች የሚያወጣውን አላስፈላጊ ወጪ በመቀነስ ምርታማነት እንዲጨምር ይረዳል። ስለዚህ ይህ የአሰራር ስርዓት በዓለም አቀፉ የንግድ መድረክ ተወዳድሮ ለማሸነፍ እንደ አንድ መሳሪያም የሚያገለግል ስለሆነ የአሰራር ስርዓቱን መትከል የተቋምን ህልውና አደጋ ውስጥ እንዳይገባ ይከላከላል።
ይህ ደረጃ ከጥራት ሥራ አመራር ስርዓት (ISO፡9001 Quality Management System) እና ከአካባቢ ደህንነት ሥራ አመራር ስርዓት (ISO 14001 Environmental Managmnet System)የአሰራርስርዓቶችጋርተመጋጋቢና ወቅቱን በጠበቀ መልኩ ያለምንም ችግር ቀላል በሆነ መንገድ ተሳስሮ ሊተገበር የሚችል ሲሆን ደረጃው በሥራ አካባቢ ከሥራ ጋር በተያያዘ የሚደርሱ አደጋዎችን በመለየት የአደጋ ተጋላጭነትን ለመቀነስና ለማስወገድ የምንጠቀምባቸው ዘዴዎች የሚያመላክት የሥራ አመራር ስርዓት እንጂ በምርት አጠቃቀምና ጥበቃ ላይ ያተኮረ አይደለም። በተጨማሪም ይህ የአሠራር ሥርዓት ከሌሎች በተቋሙ በትግበራ ላይ ካሉ ደረጃዎችና ሰነዶች ጋር የሚጣረስ ሣይሆን በቅንጅት ለመተገበር የበለጠ ዕድል የሚሰጥ ነው። ስለሆነም ደረጃው ተዓማኒነት ከመፍጠሩም ባሻገር የምርትና አገልግሎት ጥራትን ለማሳካት ቁልፍ ሚና ይኖረዋል።
(ምንጭ ISO focus November 2015 edition page 40)
ኢንቨሰትመንትና የተስማሚነት ምዘና
አንድን ምርት ወይም አገልግሎት ወደ ተጠቃሚ ከመድረሱ በፊት ጥራትና ደህንነቱ በተስማሚነት ምዘና ሥርዓት ማለፍ የግድ ይላል፡፡ ይህም መዋለ ነዋዪን ለሚያፈስ አካል ወጪን ያላግባብ እንዳያወጣ የሚረዳው ብቻ ሳይሆን ምን ያህል ወጪ በምን ያህል ጊዜ የሚለውንም ይመልሳል፡፡ የምርቶችን የጥራት ደረጃ የማረጋገጥ ተግባራት የሚከውኑ የተስማሚነት ምዘና ድርጅቶች በመንግስትም ሆነ በግል የሚከናወን ተግባር ሆኖ የዚህን ውጤታማነት የሚያረጋግጡ አካላትም ይኖራሉ፡፡ ወጪ ቆጣቢ በሆነ መልኩ መዋለ ነዋይ ለማፍሰስ ደግሞ ዓለም አቀፋዊ ተቀባይነትና ዕውቅና ያለው የተስማሚነት ምዘና አገልግሎቶችን መጠቀም ወሳኝ ነው፡፡
ይህም ጉዳይ የድርጅቱን ህልውና የሚወስን ይሆናል፡፡ አምራቾች ምርቱን በሚያመርቱበት ፋብሪካ የጥራት ክትትልና ቁጥጥር ቡድን ቢኖራቸውም 3ኛ ወገን የጥራት ማረጋገጫን መያዝ ለድንበር ተሻጋሪ የንግድ መድረክ ምትክ የሌለው ሚናን ይጫወታል፡፡ ይህንንም ማረጋገጫ መጠቀም ከወጪና ትርፍ አኳያ ሲታይ በጥቂት ወጪ ብዙ ማትረፍ ያስችላል፡፡ ሸማቹ አካል ደግሞ በተስማሚነት ምዘና ጥራቱ የተረጋገጠና ያልተረጋገጠን ምርት ለመለየት የጥራት ማረጋገጫ ሠርተፊኬቶችን ስለሚጠቀም አምራቹ የምርቱን ጥራት በራሱ አቅም ከመፈተሹ ጐን ለጐን በነፃና ገለልተኛ 3ኛ ወገን ማስፈተሹ አሳማኝ ምስክሩ ብቻ ሳይሆን ከአላስፈላጊ ወጪና ኪሳራም ይታደጋል፡፡
የሚያስገኘውም ጥቅም ዘርፈ ብዙ ሲሆን በዋነኛነት ደግሞ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳና የምርት ጥራትን ካለመጠበቅ ከሚከሰቱ የማህበረሰብ ጤናና የአካባቢ ደህንነት ችግሮች መታደግ መቻሉ ነው፡፡ ከዚሁ ጐን ለጐን በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያለው የተስማሚነት ምዘና ስራዎችን የሚተገብሩ ተቋማትን ለይቶ አብሮ መስራት ከሀገር ውስጥ የንግድ መድረክ ባለፈ ለዓለም አቀፉ ንግድ እንደ ድልድይ ያገለግላል፡፡
የጥራት ሥራ አመራር ሥርዓት (ISO 9001) ምንነትና ጥቅሞቹ
የጥራት ሥራ አመራር ሥርዓት (ISO 9001) ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው መለኪያ መስፈርት ሲሆን ምርቶች ወይምአገልግሎቶች የጥራት ደረጃቸው ዓለምአቀፍ ተቀባይነት እንዲኖረው ያስችላል፡፡እንዲሁም የስራ አገልግሎቱ ወይምምርቱ ደንበኛን በሚያረካ መልኩእንዲካሄድየአሠራር ሥርዓትን ተከትሎእንዲከወን የሚያስችል ሂደት ነው፡፡
የISO 9001 ዋናዋና ፋይዳዎች:-
- ለሁሉም ምቹ የውድድር መድረክ መክፈቱ
- የውጪ ንግድ እና ወይም አገልግሎት ማመቻቸቱ
- የተሻለ ተሞክሮን ማሳየቱ
- ለንግድእና ወይም አገልግሎት የብቃት አሰራርን ማሳየቱ
- መተማመን መፍጠሩ፤ እንዲሁም አዳዲስ የንግድ አማራጮች መያዙ
- የምርት መለያን በዓለም አቀፍ እንዲታወቅ ማድረጉ
- የጋራ መግባቢያ ቋንቋ በተቋም ውስጥም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ መፍጠር መቻሉ፡፡
ዓለም አቀፋዊ ዕውነታዎች
- ከ1,000,000 ድርጅቶች በላይ በአለም አቀፍ ደረጃ የISO 9001 ሰርቲፊኬት ተጠቃሚዎች ናቸው
- በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያለው መሆኖ
- የተለያዩ ድርጅቶች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ያደርጋል
- አንድ የሰው ኃይልያለው ተቋምም ቢሆን ሰርቲፈይድ መሆን ይችላል
የምግብ ደህንነትና ጥራቱን የማረጋገጥ አስፈላጊነት
ነፃ ገበያ የፈጠረው የዓለም የወቅቱ የግብይት ስርዓት የንግድ ልውውጥ ያለ ገደብ እንዲካሄድ ቢፈቅድም በተለይም ኢንዱስትሪ መር በሆኑት ሀገራት የምግብ ደህንነትና ጥራት ከዋጋው በላይ ከፍተኛ ትኩረት እየሰጡት ይገኛሉ፡፡ ይህም የሚያመለክተው ሀገራት ከምርት ብዛት ወደ ምርት ጥራት የአሰራር ሥርአት አምራቾች እንዲቀየሩ አስገዳጅ ሁኔታዎችን እየፈጠሩ መሆኑን ነው፡፡
በዚህ ዘመን የአመራረት ዝንባሌ በዓለም አቀፍ ገበያ ተመራጭና ተወዳዳሪ ሆኖ ለማሸነፍ ከምርቱ ጥራት ባልተናነሰ፣ ምርቱ የሚገኝበት አካባቢና የሚመረትበት መሣርያ እንዲሁም መለያው ለተፈላጊነቱ ቁልፍ ሚና እየተጫወቱ መገኘታቸው ነው፡፡ ምግብ በሚደጐምባቸው እንዲሁም የላላ የቁጥጥር ስርዓት ባላቸው ሀገራት ሳይቀር ጥራትና ደህንነት በገበያ ለማሸነፍ ወሳኝ እየሆኑ ይገኛሉ፡፡
በተጨማሪም ከማደግ ጋር ተያይዞ በሚመጣ የፍላጎት መጨመር የተነሳ የምርት ጥራት መስፈርቶች እንዲበራከቱ ምክንያት ሆኗል። የማህበረሰብ ጤናና የአካባቢ ደህንነት የወቅቱ አንገብጋቢ ጉዳዮች በመሆናቸው የምርት ጥራትን ማረጋገጥ የሀገራት ቁልፍ ተግባር እየሆነ መጥቷል።
በተለይ የግብርና ውጤቶችን አስመልክቶ ፍላጐቱ እያደገ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ አዳዲስ መስፈርቶችን ሀገራት በማውጣት የምርት ጥራትንና ደህንነትን ለማረጋገጥ በማያቋርጥ እንቅስቃሴ ላይ እንደሚገኙ ነው። ይሕም ለአምራቹ፣ በኢንዱስትሪ አቀነባብሮ ወደ ገበያ ለሚያወጣው እንዲሁም የምርቶች ጥራት ላይ ለተሰማራው ባለሙያ እንደ መልካም አጋጣሚ ይቆጠራል፡፡ ለዚህም ሀሳብ እንደ ምሳሌ ለምግብነት የሚውሉ የእንስሳት ተዋፅኦን በተለይ የስጋ ምርቶችን ስናይ የምግቦቹ ጥራትና ደህንነት እንዲረጋገጥ ሀገራት አስገዳጅ የጥራት ቁጥጥር እንዲከተሉ አስገድዷል። ገና ከጅምሩ የቁጥጥር ሥራቸውን በማጠናከር በእርድ ወቅት እና ከእርድ በኃላ በምግብ ውስጥ ሊፈጠሩ የሚችሉ ጐጂ ተህዋሲያን እንዳይፈጠሩ ልዩ ትኩረት በመስጠት የችግሩን አሳሳቢነት ለመቀነስ ቀጣይነት ያላቸው የቁጥጥር ተግባራት እየፈጸሙ ይገኛሉ፡፡